Page 5

500 BC በመጀመሪያ ሙካሪብ የተሰኙት የሳባ ገዥዎች፣ መንግሥታዊና ሃይማኖታዊ ሥልጣን አጣምረው የያዙ መሪዎች ነበሩ። ኋላ በ5ኛውና በ4ኛው ዓመተ ዓለም ላይ፣ ሥልጣኑ ዓለማዊ ሆነ።  የሳባ መንግሥት በንግድ አማካይነት ወደ አፍሪካ አህጉር መስፋፋት የጀመረው በዚህን ወቅት ሳይሆን አይቀርም። እንደዚሁም ሳባውያን ነጋዴዎችና መንደር ቆርቋሪዎች ቀይ ባህርን ተሻግረው ማዶ ባለው ቀበሌ ላይ መስፈር የሚጀምሩት በዚህን ወቅት ነው። ይህ ከአረቢያ ወደ ዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጠረፍ የሚደረገው ፍልሠት ቀስ በቀስ የማያቋርጥ ንቅናቄ ሆኖ ይቀጥላል። *15, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ   

200 BC በደቡብ ዓረቢያ በቀይ ባሕር ጠረፍ ላይ፣ በዛሬዎቹ የመንና ኤደን ምድር አካባቢ፣ ዓረቢያ ፌሊክስ – “ዕድለኛዋ ዓረቢያ”- ተብሎ በሚጠራው ደቡባዊ ክፍል፣ አስደናቂ የሆኑ የከተማ መንግሥት ሥልጣኔዎች ያበቡበት ዘመን ነበር። ከክርስቶስ ልደት በፊት በ1ኛው መክዘ ውስጥ በዚህ አካባቢ ፣ ከፍ ካለ የኤኮኖሚያዊ ፖለቲካዊና ባህላዊ ብልፅግና ደረጃ ላይ የደረሱ፣ ለበላይነት እርስ በርሳቸው የሚታገሉ ማይን፣ ካታባን፣ ሳባ እና ሃድራሙት የተባሉ መንግሥታት ነበሩ። ….ሳባ ለረጂም ጊዜ የበላይነቱን ይዛ ቆይታለች። *15, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ    

ቀስ በቀስ ግን ባለማቋረጥ የገባው የደቡብ ዓረቢያ ሕዝብ ቁጥሩ እየበዛ ሲሄድ፣ በአፍሪካው አህጉር የባህር ጠረፍ ላይ እየተሰባሰበ በመንደር መኖር ከጀመረ በኋላ ፣ ባህር ማዶ ከሚገኘው እናት አገሩ ጋር ጥብቅ የንግድ ትስስር ይመሠርታል። የአፍሪካው አህጉር በዚያን ጊዜ በጣም ተፈላጊ የነበሩ ፣ እንደ ዝሆን ጥርስ፣ ቅመማ ቅመምና የሙጫ ተክሎችን የመሳሰሉ ሸቀጦችን ላኪ ነበር።… በ ፩ኛው መቶ ዓመተ ዓለም ውስጥ፣ በትላልቅና በትናንሽ ስብስቦች እየሆኑ ፣ የዳበረ የቴክኒካዊና መንፈሳዊ ሥልጣኔአቸውን ይዘው የመጡት እነዚህ የደቡብ ዓረቢያ ሰፋሪዎች፣ በዓይነቱ ላቆጠቆጠው የኢትዮጵያ ሥልጣኔ የመሠረት ደንጊያ ጣሉ። ኢትዮጵያ ከእስልምና በፊት የነበረውን የዓረብ ዓለም ሥልጣኔ በሚወክሉት በነዚህ መሥራቾች አማካይነት ከሴማዊው ሥልጣኔ ጋር የምት ተሳሰር ሲሆን፣ ይህ ሥልጣኔ በሥፍራው ከነበረው ከኩሳ (ኩሽ) ሕዝቦች አፍሪካዊ ሥልጣኔ ጋር ተቀላቅሏል። *15, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ   

200 BC በቀይ ባሕር ዳርቻ በዙላ ባሕረሰላጤ የሚገኘው የአዶሊስ ወደብና የዳህላክ ደሴቶች ለአክሱም ሥልጣኔ መነሳትና መፋፋም ዋና ማዕከል ነበረ። አዶሊስ ለ700 (ከ150 ዓመት ዓለም እስከ 650 ዓመት ምህረት) ዓመታት ገደማ ያህል የከፍተኛ ባህልና ንግድ መሳለጫ ወደብ ሆና በመካከለኛው ባህርና በሩቅ ምሥራቅ ሕዝቦች፣ እንዲሁም በሁለቱም የቀይ ባሕር ዳርቻ አገራት መካከል ታላቅ የሥልጣኔ አስተዋፅዖ ስታስተናግድ ኖራለች ። አዶሊስ በራስ ገዝ ብቃቷ ገናናውን አክሱማዊ ሥልጣኔን አዋልዳና አሳድጋ አልፋለች። ከእስልምና ሃይማኖት ውልደትና ኃያልነት በተያያዘና ምናልባትም በመጨረሻ በድንገተኛ የውሃ መጥለቅለቅ አደጋ ምክንያቶች ከስማለች። ለአክሱም ሥነመንግሥትና ሥልጣኔ መፋፋም አዱሊስ መሠረታዊ ምክንያት ነበረች። ነገር ግን፣ የአዱሊስና የአክሱም የኢኮኖሚ ዕድገትና ሥልጣኔ ተመሳሳይ ዕድል ገጠማቸው።   

150 BC በአንደኛው ክፍለዘመን  የግሪክና ግብፅ ተወላጁ ኣርቲሜደሮ የተባለ መርከበኛ ነጋዴ፣ “ፐሪፕለስ ኦፍ ዘ ኤርትሪያን ሲ” በተባለው ጥንታዊ መፅሃፉ ላይ ስለ አዱሊስ የፃፈው ታላቅ ታሪካዊ ማስረጃ ሆኖ ይገኛል። መፅሃፉ በአፍሪካ ቀንድ አዱሊስ ብቸኛና አብይ የንግድ ወደብ በመሆን የግብፅ ፋራዕኖች ፍላጎትን ከህንድ፣ ሩቅ ምሥራቅና አፍሪካ ድረስ መጋቢ ወደብ ጭምር እንደነበር ዘግቦታል።እንደ ጣሊያናዊው የከርሰምድር ጥናት ተመራማሪ ከሆነ፣ የአዱሊስ ወደብ ከተማ ከነ ነዋሪዎቿና ጥንታዊ ቅርሷ፣ በ7ኛው ክፍለዘመን ላይ በድንገትና በቅፅበት ከቀይ ባሕር በተነሳ የውሃ ግድግዳ ተጠለቅልቃ ጠፍታለች።  ከቀይ ባሕር ወለል ሥር በድንገትና ሳይገመት በተከሰተተው የመሬት መንቀጥቀጥ ምክንያት የተፈጠረው ግዙፍ የውሃ ግድግዳ በ6 ኪሎሜትር ርቀት ላይ የምትገኘውን የ አዶሊስ ወደብና ከተማ ከምድረ ገፅ አጠፋት። ይህች ዕጣ ፈንታዋ በአሳዛኝ የተፈጥሮ አደጋ የተወሰነላት ሥፍራ፣ ጥንታዊቷ አዱሊስ ከተማ፣ ብዙ ሺህ ዓመታትን በአፍሪካ ቀንድ ለተከሰተው ሥልጣኔ አብይ የንግድ መናኸሪያ እንደነበረች ለማስታወስ ግብፃውያኑ ፈርዖኖች ከድንጋይ ተሰርቶ የተፃፈበት የአስከሬን ሳጥናቸው ላይ የፑንት ዋና ከተማና የአምላካት ምድር እያሉ እስከዛሬም በቅርሶች ላይ ዘግበውት ያስነብባሉ።    

100 BC የኢኮኖሚያዊ አቋማቸው ከተሻሻለ በኋላ፣ እነዚህ የደቡብ ዓረቢያ ሰፋሪዎች ወደ ደቡብ ምዕራብ አቅጣጫ መስፋፋት ይጀምራሉ። አዲሱ ሕዝብ እያደር ከደቡብ ዓረቢያው እናት አገር ቁርኝቱ እየተላለቀ ይመጣና አንድ ራሱን የቻለ፣ የራሱ የሆነ የማህበራዊና የሥልጣኔ አደረጃጀት ያለው ተቋም ሁኖ ይወጣል። ….  ከ1ኛው መክዘ ጀምሮ፣ አዲሱ የዘሮች ውሁድ የሆነው ሕዝብ፣ ከደቡብ ዓረቢያ መንግሥታት ነፃ ሁኖ ራሱን ችሎ መቆም ይጀምራል። የዚህን ሕዝብ ዕድገት የሚገታ አንዳችም ውስጣዊ እንቅፋት አልነበረም፣ የውጪውም ሁኔታ አመች ነበረ። የመልካ ምድራዊ አቀማመጡ አመቺነት ለዚህ አስተዋፅዖ አድርጓል። ምክንያቱም ይህ ቀበሌ በዓረቢያና በመውደቅ ላይ በነበረው የሜሮዔ ንጉሣዊ መንግሥት መካከል ለሚካሄደው ንግድ ዋና አገናኝ አንጓ በመሆን ነው።  *17, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ 2003  


 ከ1ኛው መክዘ ጀምሮ፣ በዛሬይቱ ኢትዮጵያና ኤርትራ ሰሜናዊ ክፍል፣ ከዓረቢያ የመጡት ሰፋሪዎች የፈጠሩት፣ ልክ በእናት አገራቸው አምሳያ የተደራጀ አንድ ጠቅላይ ግዛት ነበረ። ከክርስቶስ ልደት በፊት አያሌ ምዕተ ዓመታት ቀደም ብሎ ባለው ጊዜ ውስጥ የሚወድቀው ይህ ጠቅላይ ግዛት የተመሠረተበት ወቅት፣ የሳባዊ ዘመን ተብሎ ይታወቃል። ሰፋሪዎቹ በአዲሱ አገር ውስጥ ቀስ በቀስ ጥንካሬ ያገኙትና እንደ አይቀሬነቱም በሥፍራው ያለው ኩሻዊ ሕዝብና ሥልጣኔው ከውጭ ከጎረፈው ከሴማዊው ጋር መቀላቀል የሚጀምረው በዚህን ወቅት ሲሆን፣ የመጤዎቹ ቴክኒካዊ ባህላዊ ሥልጣኔ ደረጃ ከዚህኛው ከፍ ያለ ስል ነበረ፣ በውህደቱ ሂደት ላይ የበላይነቱን ሚና ተጫውቷል። *17, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ 2003  

26 BC አውገስተስ የተባለው የመጀመሪያው የሮም ንጉሠ ነግሥት ሮምን ከዓለም በውበቷ ተወዳዳሪ የሌላት ከተማ አድርጎ ለመሥራት ተነስቶ ሥራ ጀመረ። በጣም ውድና በሥነ ህንፃ ጥበብ የረቀቁ ቤተ ዕምነቶችና፣ በኋላ በማንኛውም የሮም ግዛት ከተሞች የሮማውያን ፎረምስ በመባል የታወቁትን ባለዓይነተኛ ኣርችና ምሶሶ ህዝባዊ ማዕከሎችን አስፋፋ።  እነዚህ ፎረም የተባሉት የከተማ የሕዝብ መሰብሰቢያ ማዕከሎች የሮም ዜጎች የንግድ፣ የዕምነት፣ የፖለቲካ ምርጫ ማካሄጃ፣ ወታደራዊ ድልን ማክበሪያና ጓደኛማቾች የሚገናኙበት ድንቅ ቦታ ነበር። በሮም በዓይነቱ ከሁሉም ያላቀ ጠቀሜታ የነበረው ደግሞ ፎረም ሮማነም ይባል ነበር። በጣም ዕውቅ ከሆኑት የሮማውያን ህንፃ ውስጥ አንዱ፤ ኮሎሲየም የተባለው ስታዲዮም መሳይ የጦረኛና ተጋዳይ አካላት ትዕይንተ መድረክ ነው። ሮማውያን ምርጥ ኃውልቶችንና ባለ ኣርች ህንፃዎችን ገንብተዋል። ኮንክሪት ተጠቅመዋል። ለግዛት ወታደሮቻቸውንና ንግድን ለማሳለጥ ረጂም ዕድሜ ያላቸው መንገዶችን ሠርተዋል፣ ውሃና ፈሳሽን በርቀት ማዳራሻ መንገድ ወይም ከፍ ያለ የውሃ ድልድይ መስመር፣ እንዲሁም የሕዝብ የጋራ ሽንት ቤቶችና የሠውነት መታጠቢያ ክፍሎችን በከተሞቻቸው ሠርተው ነበር።  

በዚያን ጊዜ ቀይ ባህር በከፍተኛ ደረጃ በሄለናዊ (ግሪክ) ሥልጣኔ እቅፍ ውስጥ የሚገኝ ቀበሌ ነበር። ስለዚህም አክሱም ሰፊ የንግድ እንቅስቃሴ ያለው መንግሥት ነበርና ከዚህ ሥልጣኔ ሱታፌ ውጭ አልነበረም። አባ ጰንጠሌዎን ላይ የተገኙት የግርክኛ የደንጊያ ላይ ፅሁፎች፣ የሄለናዊ ሥልጣኔ በዚያን ጊዜ አክሱም ላይ ተስፋፍቶ እንደነበረ አሳማኝ ምስክሮች ናቸው። በወቅቱ አገሪቱን ተዘዋውረው የጎበኙ ግሪኮች በጻፏቸው ድርሳኖች፣ የአክሱም መሪዎች ግሪክኛ ቋንቋን አቀላጥፈው ይናገሩ እንደነበረ ገልጸዋል። የአክሱም ከተማ መልካምድራዊ አቀማመጥ ለሀገረመንግሥት መናገሻነት ምርጫነቷ ትልቅ አስተዋፅዖ አበርክቷል። ከተማዋ ከባህር ወለል 2ሺ ሜትር ገደማ (6,562 ጫማ)፣ በኮረብታ አናት ላይ ትገኛለች። የአየር ንብረት፣ ዝናብ መጠን፣ የለም አፈር ይዞታው እንስሳትንና እርሻን ለማሳለጥ እጅግ ምቹ ነበር። ከሁሉም በበለጠ ጠቃሚነቱ ግን፣ የከተማዋ ስልታዊ አቀማመጥ ቅቡልነት ቁልፍ የሆነ መስቀለኛ የንግድ ዝውውር መስመር ላይ መሆኑ ነው።  አክሱም የባህር ጠረፍን ከውስጣዊው የአፍሪካ ክፍሎች ጋር የምታገናኝ ከፍተኛ የንግድ ማዕከል ሆነች።      

የቅድመ ክርስትናው አክሱማዊ ዘመን፣ ከተቀዳሚው ከሳባዊው ዘመን (አሃዱ አክሱማዊ ተብሎም ይታወቃል) የሚለይባቸው አንዳንድ ነገሮች አሉ። በመጀመሪያ ደረጃ የድርጅታዊ አቋም መጠናከር፣ ራስን የመቻል ብቃት መጨመርና፣ እያንዳንዱ የመጤ ስብስብ ከነባሩ ሕዝብ ጋር ተቀላቅሎ የፈጠረውን የራስን ሥልጣኔ የማዳበር ሂደት ይመጣል። ቀጥሎ አክሱም፣ በመውደቅ ላይ ባለችው በሃብታሟ  ሜሮዔና በዓረብ ባሕረ ሰላጤ መካከል የሚገኝ መንግሥት በመሆኑ ሁኔታው ስላመቸው፣ በኤኮኖሚ ለመበልፀግና በአፍሪካ ምድር ላይ ግዛት ለማስፋት የመብቃቱ፣ በመጨረሻም መንግሥታዊ ሥልጣን በአንድ ተማክሎ፣ መሪዎቹ አክሱምን መቀመጫቸው አድርገው በመቆርቆር ተሰሚነታቸውን ያጠናከሩበት ሁኔታ ታይቷል። *18, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ  

ናፓታና መርዌ ከግብፅ እንደመዋሰናቸው መጠን ቋንቋቸው፣ ፊደላቸው፣ ሃይማኖታቸው ከግብፅ ጋር የተወሰደ ነው። አክሱም ደግሞ ወደፊት እንደምናገኘው ከዐረብ አገር ጋር ጎረቤት ስለሆነ በአክሱም ከነዋሪው በቀር በገዢነት የተመሠረቱት ከደቡብ ዐረብ ከሳባ፣ ከሐበሳት፣ ከሒሚያሪያት የመጡ ነገዶች ስለሆኑ ቋንቋቸው፣ ጽሕፈታቸው፣ ልማዳቸው ከደቡብ ዓረብ የተወረሰ ሆኖ ይገኛል። ደቡብ ዐረብ ደግሞ ይህን አክሱሞች የወረሱትን ሥልጣኔ ከየት አገኘው  ተብሎ ሲመረመር፣ ከባቢሎንና ከአሶር ሆኖ ይገኛል። ይኸውም ማለት ከመካከለኛው ምሥራቅ (አሶር፣ ባቢሎን፣ ከለዳውያን፣ አካድያን) በየጊዜው ከደቡብ ዐረብ መጥተው ሲኖሩ ከዚያ ደግሞ የኤርትራን ባሕር እየተሻገሩ ወደ ኢትዮጵያ ገቡ የነርሱም (የሳባ ፊደል) ፊደልና ቋንቋ፣ ሃይማኖትና ልማድ ከአሶራውያንና ከአካድ ሲመሳሰል ከናፓታዎችና ከመርዌዎች ከግብፆች ፊደልና ቋንቋ፣ ሃይማኖትና ልማድ፣ ከአሶራውያንና ከአካድ ሲመሳሰል ከናፓታዎችና ከመርዌዎች፣ ከግብፆች (ሂዩሮግሊፍ) ፊደልና ቋንቋ ጋር በፍፁም የተለያየ ነው። …. *185፣ተክለፃድቅ መኩሪያ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት፣ 1951   

ከ5ኛው እስከ 1ኛው መቶ ዓመተ ዓለም አካባቢ ድረስ ያለው ጊዜ፣ ከደቡብ ዓረቢያ ፈልሶ የመጣው ሕዝብ ከእናት አገሩ ጋር ያለውን ጥብቅ ትስስር ጠብቆ ፣ ከአፍሪካ ምድር ጋር መዋህድና ድርጅታዊ ኢኮኖሚያዊ አቋሙን ማጠናከር የጀመረበት ወቅት ነበር። መቀሌ ላይ በተገኘ አንድ የደንጊያ ላይ ፅሁፍ፣ የሳባ የሃይማኖታዊና ዓለማዊ ገዥዎች ይጠሩበት የነበረው “ሙካሪብ” የሚለው የማዕረግ ስም ተጠቅሶ ይገኛል። በበሬ አምሳል ተቀርጾ በዓረቢያ በስፋት ይታወቅ የነበረው አልማካህ (ወይም ኢሉምክ) የተሰኘው የጨረቃ አምላክ፣ በአፍሪካ ምድር ከዋና ዋናዎቹ ዝነኛ አማልዕክት አንዱ ነበር። አጋሜ ውስጥ ለዚህ ጣዖት የቆመ ቤተ ቁርባን፣ ሃውልቲ መላዞ ላይ ደግሞ ቤተ መቅደሱ ተገኝቷል። የሃ ላይ በቁፋሮ የተገኙት ሃውልቶች ፣ በሳባ ዘመነ መንግሥት በዚህ ሥፍራ አንድ ዋና የሃይማኖታዊ ማዕከል ይገኝ እንደነበረ የሚያመለክቱ ናቸው። *16, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ 2003  

የሃ ላይ በቁፋሮ የተገኙት ሃውልቶች፣ በሳባ ዘመነ መንግሥት በዚህ ስፍራ አንድ ዋና የሃይማኖታዊ ማዕከል ይገኝ እንደነበረ የሚያመለክቱ ናቸው። የሃ ላይ ምንም ያህል ያልተበላሸ የሚያምር ቤተ መቅደስ፣ የግድግዳ ስዕሎች፣ የቁርባን ገበታዎች፣ ከጥርብ ደንጋይ የተሠራ የመቃብር ሃውልት ላይ ጽሁፎች ተገኝተዋል። እነዚህ ሁሉ ቅርሶች ትክክለኛ የደቡብ ዓረቢያ ሥነ ጥበብ ገፅታዎች ናቸው። ግን በቁፋሮ የተገኙት ቅሪቶች ብቻ አይደሉም የዚያን ሥልጣኔ ምንነት የሚያረጋግጡት። ሰፋሪዎቹ ለቆረቆሯቸው ከተሞች በሃገራቸው የሚታወቁ ስያሜዎችን ሰጥተዋቸዋል። እስከ አሁንም ድረስ ያለው የሠራዌ (ሠራየ) ከተማ ስያሜ ለዚህ አንድ ምሳሌ ነው። እንደዚሁም ያገሪቱ መታወቂያ የሆነው አቢሲንያ የሚለው ስያሜ፣ በዓረቢያ ከሚታወቅ ሀበሻት ከተባለ የነገድ ስም የመጣ ነው። በተመሳሳይ፣ ግዕዝ የተሰኘው ጥንታዊው የኢትዮጵያ ቋንቋ፣ አጋዚ ከተባለው የሕዝብ ስም የተገኘ ነው። ሌሎችም እንደነዚህ ያሉ በዚያን ጊዜ ከቀይ ባህር ግራና ቀኝ ባለው አገር ይሠራባቸው የነበሩ ብዙ ቃላትና ስያሜዎች አሉ። *16, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ   

አዲሱ የዘሮች ውሁድ የሆነው ሕዝብ፣ ከደቡብ ዓረቢያ መንግሥታት ነፃ ሁኖ ራሱን ችሎ መቆም ይጀምራል። የዚህን ሕዝብ ዕድገት የሚገታ አንዳችም ውስጣዊ ዕንቅፋት አልነበረም፣ የውጭውም ሁኔታ አመች ነበር። …. የኢኮኖሚያዊ አቋማቸው ከተሻ ሻለ በኋላ፣ እነዚህ የደቡብ ዓረቢያ ሰፋሪዎች ወደ ደቡብ ምዕራብ አቅጣጫ መስፋፋት ይጀምራሉ። አዲሱ ሕዝብ እያደር ከደቡብ ዓረቢያው እናት አገሩ ቁርኝቱ እየተላቀቀ ይመጣና አንድ ራሱን የቻለ፣ የራሱ የሆነ የማህበራዊና የሥልጣኔ አደረጃጀት ያለው ተቋም ሁኖ ይወጣል።   ከዚህ ወቅት በኋላ፣ ለ አምላክ አልማካህ የሚቆሙ ሃውልቶች የሳባዊው ትክ ክለኛ ቅጂ መሆናቸው ይቀራል። በዚህ ፈንታ፣ ዛሬ የ ኢትዮጵያ መለያ ሁኖ የሚታወቀው የባለሻኛ በሬ ምስል ተተካ። ግዕዝ በ አፍሪካው የቀይ ባሕር ጠረፍ ተውልዶ ያደገና፣ ከሳባዊኛው ጋር የተዛመደ ጽሑፍና ቋንቋ ሲሆን፣ ቀስ በቀስ የሳቢኛውን  ጽሑፍ ተክቶታል። እነዚህ ነገሮች አንድ ራሱን የቻለና አንድ ወጥ የሆነ ሥልጣኔ ለመፈጠሩ ማረጋገጫዎች ናቸው። ካሁን ወዲያ መሪዎቹ ሙካሪብ የሚለውን ስያሜ ትተው፣ ንጉሠ ነገሥት ተብለው መጠራት ጀመሩ።  *17-18, የኢትዮጵያ ታሪክ , ባርትኒስኪና ኒየችኮ 2003    

 

 

Page 4

Page 4 START 

በፍልሠት ከተለያዩ ሥፍራዎች መጥተው የተዋሃዱት ኢትዮጵያዊ ከመሆናቸው አስቀድሞ በምድረ ኢትዮጵያ የነበሩትን ሕዝቦች፣ በሚከተለው ሰንጠረዥ የምድረ ኢትዮጵያ ነባር ሕዝብ ተብለው ታሪክ ይዘታቸው የሚከተለውን ይመስላል። 

34-35፣ የጥንቷ ኢትዮጵያ ትንሣኤ ታሪክ፣ መራሪስ፣ 1985 

በዚህ በ፲ኛው፣ በ፱ኛውና በ፰ኛውም መቶ ዓመት ከክርስቶስ ልደት በፊት በሰሜን ኢትዮጵያ በኋላ የገነነውና አሁን ገናንነቱን በሐውልቱና በጽሑፉ የምናውቀው የአክሱም መንግሥት እስከአሁን  አለመነሣቱን የሳባውያንና የአክሱምን ታሪክ የመረመሩት ሊቃውንት ሁሉ አረጋግጠዋል። ከአትባራ ወንዝ ወዲያ በኑብያ ግን እነዚያው በኢትዮጵያነት የምንጠራቸው መጀምሪያ ነፃ ሆነው፣ በኋላ እነቱትሞሲስ ቀጥሎም እነራምሲስ ፪ኛ ካስገበርዋቸው ወዲህ አሁንም አንዳንድ ጊዜም እነሱ እያጠቁ፣ አንዳንድ ጊዜም በግብፅውያኑ እየተገዙ ኑሯቸውን ይቀጥላሉ። *78፣ተክለፃድቅ መኩሪያ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት፣ 1951  

ከድዓማት እስከ አክሱማዊ ሥረወ መንግሥቱ ተመሥርቶ ገናና ለመሆን እስከበቃበት ጊዜ ድረስ ያለው ታሪክ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብን ኤኮኖሚያዊና ማህበራዊ ህይወት በተጨባጭ ታሪካዊ የማስረጃ ቅርስ በተገቢው መጠን ባልተዘጋጀበት፣ ስለ ድዓማት ዘመን ኤኮኖሚያዊና ማህበራዊ ህይወት ታሪክ በዋና ትኩረትነት ለጊዜው ብዙ ማለት አይቻልም። ከዚህም የተነሳ በዋናነት የዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ታሪክ የፖለቲካና መንግሥታዊ ሥልጣኑን ከንግሥተ ሳባ ጀምሮ ሲረካከቡ ከመጡት ነገሥታት ስምና የሥልጣን ቆይታ ዘመናቸው ብዙም ያለፈ ሆኖ አልተገኘም።  የተሻለ ቅርሳዊ ኤኮኖሚያዊና ማህበራዊ ህይወት ማስረጃዎች በአሁኑ ትውልድ ሥራ  እስከሚጨመርበት ጊዜ ድረስም ቢሆን ፖለቲካዊና መንግሥታዊ ሥልጣን የያዙትን የድዓማት ሥርወመንግሥት መሪዎች ስምና የሥልጣን ዘመን እናያለን።  እዚህ ላይ አንባብያን የራሳቸውን ከፍተኛ ጥንቃቄና ጥናታዊ ሥራዎች ምርምር ቢሠሩ ይመከራል። ለጊዜው በቂ የአርኪዮሎጂና ሌሎች ሳይንሳዊ የታሪክ ማስረጃ ምንጮች እንደሌሉም መገንዘብ ግድ ይሆናል።    

የናፓታና የአክሱም አገሮች በአገር ጉርብትናም በዘርም የሚገናኙ ሁለቱ በየተራ የገነኑ ወንድማማቾች ናቸው። ሁለቱ አገሮች በመልክ፣ በቅርፅ፣ በደም ግባት፣ በአገር ካርታ አቀማመጥ በሥርዓትና በልማድ በቤትና በዕቃ፣ በጦር መሣሪያ በሙሉም ባይሆን በመጠኑ ተመሳስለው፣ ተከላልሰው ይገኛሉ። *183፣ተክለፃድቅ መኩሪያ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ኑብያ፡አክሱም ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት፣ 1951   

በመዠመሪያ ናፓታ፣ ቀጥሎ መርዌ በገነነበት ሰዓት በአክሱም ዙሪያ የሚገኘው አገር በነርሱ መገዛቱ፣ አክሱም በገነነ ጊዜ ደግሞ አብርሃና (ኢዛና) ተከታዮቹ ኑብያን (ናፓታና መርዌ) መግዛታቸው የታወቀ ስለሆነ ይህ የእርስ በርስ መገዛዛት አንድነታቸውን ጭምር ያስረዳል። በዚሁ የተነሣ አብዛኛው ጸሐፊ ሁሉ ይልቁንም ያገራችን ሊቃውንት ከአክሱም በፊት በናፓታና በመርዌ የነገሡትን ነገሥታት የኢትዮጵያ ነገሥታት እያደረገ ዝርዝራቸውን ከነስማቸው ከአክሱሙ ነገሥታት ጋር ተርታ እየሰጠ ይፅፋል።  *184፣ተክለፃድቅ መኩሪያ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ኑብያ፡አክሱም ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት፣ 1951   

እንግዲህ ጥንታዊ ኢትዮጵያን እንደ አንድ ሳንቲም መስሎ መግለፁ ጥንታዊ ኢትዮጵያ አንድ አካልነትን ይዛ በሁለት የአንድ ሳንቲም ገፅታዎች የምትገለፅ አገር እንደነበረች በቀላሉ ለማሳየት ይረዳል። ከነገደ ሴም ሐረግ የሚመደበው በቀዳማዊ ሚኒሊክ አጃቢዎቹና መሪነትና ከደቡብ አረቢያ  የመጡት ነገደ ዮቅጣኖች እጅግ ሠፊ ተፅዕኖ ፈጣሪ ሆነው ከአንደኛው ጥንታዊ ምድረ ኢትዮጵያ ሲመደቡና እንደአንደኛው የሳንቲሙ ገፅታ ሲሆኑ፣ በሁለተኛው የሳንቲሙ ገፅታ ጥንታዊ ምድረ ኢትዮጵያ ደግሞ ከነገደ ካም የሚመደበው የኑብያ ኢትዮጵያ ህዝቦች ይገኙበት ነበር። በዚህ በመጀምሪያው አንድ ሺህ ዓመታቱ የጥንታዊ ኢትዮጵያ ታሪክ ተቀምጦ የምናገኘው የእነዚህ የተቀላቀሉ የሁለት ነገድ መሪዎች የጥንታዊ ኢትዮጵያን መሪነት ዝርዝር ታሪክ ይሆናል። ማለትም እንደ ከርማ፣ ናፓታና መርዌ ባሉ የነገደ ኩሽ ኑብያ  መናገሻዎችና እንደ የሃ፣ አዶሊስና አክሱም ባሉ መናገሻዎች ደግሞ ከሴምአውያን ነገድ የተዛመዱ የድዓማትና አሱማውያን ሥልጣኔ መሪዎች ዝርዝር ነው።   

ይህ ከዚህ በታች ብዙ ዘመናትን እየዘለለ ነገሥታቱን መርጦ መጥቀስ ያስፈለገው ለምሳሌነት ማሳያ ብቻ እንዲሆን በማሰብ ነው። ስለዚህ እያንዳንዱ የተዘለለው ዓመታት የራሱ መሪና በውል የታወቀ ስምና ዘመን እንዳለው ሊታወቅ ይገባል።   

930 BC አሜንሆቴፕ፣ ዘግዱር የነገሡበት ዓመታት ብዛት 41   

889 BC አክሱማይ ራሚሱ፣ ወረደ ፀሃይ  የነገሡበት ዓመታት ብዛት 20   

751 – 716 BC ፒያንኪ ፪ኛ ፣   የነገሡበት ዓመታት ብዛት 34   

716 – 701  BC ሻባካ፣  የነገሡበት ዓመታት ብዛት 15   

701 – 690 BC ሻባታካ፣  የነገሡበት ዓመታት ብዛት 12   

690 – 664  BC ታርሐቃ፣   የነገሡበት ዓመታት ብዛት 26   

664 – 656 BC ታኑታሙን፣  የነገሡበት ዓመታት ብዛት 8   

594 BC ዙዋሬንብረት፣ አስፑርታ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 41   

521 BC ሶፎልያ፣ ነኪቦን  የነገሡበት ዓመታት ብዛት 31    

423 BC አጵራሶ፣  ታልክሃርሜን የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

328 BC ናስታሴን የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

296 BC አርካሚን ፪ኛ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

233 BC ኒኮሲስ፣ ቅንዳኬ ፭ኛ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

138 BC ነግሣይ፣ ብሲኒቲ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

98 BC ሠናይ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

77 BC ዳዊት ፪ኛ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 10   

29 BC አሞይ፣ መሐሲ የነገሡበት ዓመታት ብዛት 5   

8 BC ባዚን የነገሡበት ዓመታት ብዛት 8   

*74-365 ፣ተክለፃድቅ መኩሪያ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት፣ 1951   

ለወደፊቱ፣ ከዚህ በላይ የተዘረዘሩትን የጥንታዊ ኢትዮጵያ ነገሥታት አበይት የሚባሉ ታሪኮችን ወደፊት እየመጠንን በዚሁ ዓምድ ጨምረን እናብራራለን።  እነዚህ ከሶስቱ የመጀመሪያው አንድሺህ ዓመታቱ ከሥርዓተ መንግሥቱ መሪዎች ውስጥ ጥቂቶቹ ብቻ ተለይተው  ለናሙና ዕይታ ብቻ ተመርጠው ለጊዜው  የቀረቡ ናቸው። ከዚህ በላይ እንደተገለፀውም እነዚህም ሆነ ሌሎች እንደነዚህ ያልተዘረዘሩ የኢትዮጵያ ነገሥታት የኑብያና ሳባውያን የቅይጥ ኢትዮጵያ ድምር ውጤቶች መሆናቸውን ማስተዋል ያስፈልጋል። ለጊዜው በዚህ ያልተዘረዘሩትንም ሆነ ሌሎች ተዛማጅ የወቅቱን መጠነኛ ታሪካዊ ዘገባዎች ወደፊት በሂደት እዚሁ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ የምናቀርብ መሆኑን እንገልፃለን።   

አክሱማውያን ከሴም ወገን ከወረደው ከዮቅጣን ሳባ የመጡ ሲሆኑ የኑብያ (ናፓታና መርዌ) ሕዝብ ከካምና ኩሽ፣ ከወረዱት ሳባ የመጡ ስለሆነ በአክሱሞች ዘንድ ሴማዊ በኑብያዎች ዘንድ የካምና የኩሽ ዘር ይበዛል።    

*184፣ተክለፃድቅ መኩሪያ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት፣ 1951 

 END OF PAGE 4 

Page 3

ክፍል 1፥ የመጀመሪያዎቹ አንድ ሺ ዓመታት

1013 BC ከክርስቶስ ልደት አስቀድሞ በኢትዮጵያ ከነገሡት ነገሥታት ሁሉ ንግሥተ ሳባ እጅግ ስመ ጥሩ ነበረች።…. ይኸውም እርሷ በዚያ ዘመን ከዓረብ አገር የመን የሚባለውን ጨምራ ትገዛ ነበር።…. ግዛትዋም እጅግ ሰፊ ነበር። በስተምሥራቅ እስከማዳጋስካር በስተሰሜንና በስተ ምዕራብ እስከ ምስርና (ግብፅና) እስከ ኖብ (ኑብያ) ዳርቻ፣ በስተደቡብ ዛሬ የቪክቶሪያ ባሕር እስከ ተባለው እስከ ኒያንዛ ከሚባለውም ባሕር ነጭ ዓባይ ወጥቶ ከጣና ከሚወጣው ከጥቁር ዓባይ ጋራ በካርቱም ላይ ተገናኝቶ የሱዳንንና የምስር አገሮች ያጠጣል።    * 1፣ ኅሩይ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ ከንግሥተ ሳባ እስከ ታላቁ የአድዋ ድል፣ 1927

በንግሥት ሳባም ዘመን የዳዊት ልጅ ሰለሞን በኢየሩሳሌም ንግሦ ነበር። በዚያንም ዘመን ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም የሚመላለስ ታምሪን የሚባል ነጋዴ ነበርና እርሱ በኢየሩሳሌም ያየውን የሰለሞንን ሥራ ሁሉ ስለነገራት በጆሮ ከመስማት በዓይን ማየት ይበልጣል ብላ ከአክሱም ተነስታ ወደ ኢየሩሳሌም ወረደች ። *3፣ ኅሩይ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ ከንግሥተ ሳባ እስከ ታላቁ የአድዋ ድል፣ 1927

 

የኤርትራንም ባሕር ተሻግራ (ወደ ሃገሯ ተመልሳ) በሐማሴን አውራጃ ማይበላ በሚባል አገር ስትደርስ ወንድ ልጅ ወለደች ። ስሙንም ኢብነ መለክ ብላ አወጣችለት። ትርጉሜውም የንጉሥ ልጅ ማለት ነው። በዘመን ብዛት ግን ንግግሩ እየተለዋወጠ ምኒሊክ ተባለ። የዚህም ትርጓሜ  ብልህ ልጅ ማለት ነው። *4፣ ኅሩይ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ ከንግሥተ ሳባ እስከ ታላቁ የአድዋ ድል፣ 1927

በመለኮታዊ ትርጉሙ፣ ስጦታነቱና ድንቅነቱ ተወዳዳሪ የሌለው ተብሎ በአይሁዳውያን በልዩ ስሜት ከሚታሰበው ንብረት አንዱ የሙሴ ፅላት (ታቦት)ነው። በተመሳሳይ ኢትዮጵያዊ አይሁዶች (ቤተ እስራዔላውያን) እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ንብረቱ ወደ ኢትዮጵያ የንጉሥ ሠለሞን እና ንግሥተ ሳባ ልጅ የሆነው በቀዳማዊ ሚኒሊክ አማካኝነት ወደ ኢትዮጵያ መጥቶአል ተብሎ ይታመናል። ይህ ታሪካዊ ዕምነት አወዛጋቢና ለማረጋገጥ እጅግ ፈታኝ ጥያቄ ሆኖ እስከዛሬ በዓለማችን ይገኛል።  በአክሱም በ1314 የወጣው ክብረ ነገሥት የተባለው መጽሃፍ ታሪኩን በዕውነትነት ዘግቦ አስቀምጦታል። የፅላቱን አመጣጥና በአሁኑ ዘመን የተቀመጠበትን ሥፍራ ብዙ የተለያዩ ዕምነቶችና ትንታኔዎች እንዳሉ አንባቢያን ሊያስተውሉ ይገባል። ስለዚህም በዚህ መድረክ የተቀመጡት ስለፅላቱ ትክክለኛውን አሁናዊ ዕውነታ ለማረጋገጥ ሳይሆን ከብዙዎቹ የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያህል እንዲታወቅ ይሁን። 

987 BC ሚኒሊክ ከአባቱ ጉብኝት በኋላ ወደ ሃገሩ ኢትዮጵያ ምድር ለመመለስ ሲነሳ፣ ንጉሥ ሠለሞን በሥሩ ከአሉት የገዢ መደብ ከነበሩት ከልጆቻቸው የመጀመሪያዎችን ወጣቶች ስብስብ ፈጥሮ በእንደራሴነት ከሚኒሊክ ጋር ወደ ኢትዮጵያ ሂደው የእስራዔል መንግሥትን በኢትዮጵያ ወክለው ሚኒሊክን በማገዝ በአስተዳደር እንዲመሩ አዘዘ። ከእነዚህ የሚኒሊክ አጃቢ ወጣቶች ዋናው አዛሪያህ የሚባል የእስራዔላውያኑ መንግሥት ከፍተኛ ካህን የመጀመሪያ ልጁ ነበር። አዛሪያህ የንጉሥ ሠለሞንን ትዕዛዙን ቢጠላውም መታዘዝ ነበረበት። ስለሆነም በቁጭትና ብቀላ በሚመስል መልኩ ፅላቱን ደብቆ በመስረቅ ለሚኒልክ ግማሽ መንገድ እስኪደርስ ድረስ ሳያሳውቀው ወደ ኢትዮጵያ ይዞት መጣ። 2, Bernard Leeman, The Ark of the Covenant, 2011

982 BC ንግሥተ ሳባ ልጇ ሚኒሊክ ከአባቱ በብዙ አይሁዳውያን ታጀቦ እንደተመለሰላት ባየች ጊዜ ከልጇ ጋር በዕኩል ሥልጣን ኢትዮጵያን ለማስተዳደር ተስማማች።  በተለይም በግዛቷ የሚኖሩትን ቅይጡን የሳባውያን፣ የኢትዮጵያውያንና እስራዔላውያን ሕዝቦችን ሚኒልክ ሙሉ ለሙሉ እንዲያስተዳድር ተወችለት። በዚህም መንግሥታዊ ሃይማኖቱ እስራዔላዊ ወይም አይሁዳዊ ሆነ። ድንቅ ፅላቱና (ታቦቱና) የሙሴ ህግ (የኦሪት ህግ) ማዕከላዊ የኢትዮጵያ መንግሥትና ህዝብ  ሃይማኖትም ለመሆን በቃ።  መንግሥቱም እንደ አዲስ የፅዮን ሥርወ መንግሥት ወኪልና በሳባ-ሚኒሊክ የተስፋፋ ግዛት ተቆጥሮ ጅማሮው ተቀመጠ። 3, Bernard Leeman, The Ark of the Covenant, 2011.

እናቲቱም አብረውት በአንድ ላይ ለመጡት እስራዔላውያን ጥሩ ቦታ መርጠው እንዲቀመጡ አደረገች። ሃዶራውያን የሚበዙበት የሴም ልጅ የዮቅጣን ልጆች ናቸው። የዮቅጣን ልጆች ኤል፣ ሞዳድ፣ ሣሌፍ፣ ሃስረሞት፣ ሳባ፣ አፌር፣ ኤላውጥ፣ ዩባብ ናቸው። እነዚህ ሁሉ ለዮቅጣን ተወልደውለት የዘራቸው ዘሮች በሰፋርና በማሴ መካከል ይኖሩ ነበር። እንደ አረቡ ከማሼ፣ እንደ ግእዙ ሃማሴ ወይም ማሴ ከሚባል ሃገር ተነስተው ስለመጡ የሰፈሩበትን ቦታ ሃማሴን አሉት። ገዛ የሚባል የጋዛ ሰው አለቃቸውና መሪያቸው ስለነበር ስማቸው አግአዚያን እንዲባል እብነልመለክ አዘዘ። እናቱንም ማክዳ አላት። ….አግአዚያን ማለት በግእዝ፣ ገዢዎች ነፃ አውጭዎች ማለት ነው። …. ስለዚህ የሴም ልጅ የዮቅጣን ነገዶች ቋንቋቸው ግእዝ ተባለ። ልሣነ ግእዝ ብሄረ እግዚ ወንሃነ አግአዝያን ይላል።  44-45፣ የጥንቷ ኢትዮጵያ ትንሣኤ ታሪክ፣ መራሪስ፣ 1985

ንግሥተ ነገሥት ኢትያ ልጅዋን እብነልመለክን በግዮን ወንዝ ዳርቻ እንደ አባቶቹ ህግ ወርዶ እንዲነግሥ ብትጠይቀው እንደ አባቱ እንደሰለሞን  እንደወገኖቼ እንደ እስራኤል ህግ እንጂ እንደ አንቺ ዘመዶች ሥርዓትና ህግ በወንዝ ዳር ሄጄ ሥርዓተ ንግሥን አልፈፅምም ብሎ በካህኑ ሣዶቅ ልጅ በአዛርያስ እጅ ቅባእ መንግሥት ተቀብቶ እናቱ ስትገዛው የነበረውን ከኪት እስከ ማድጋ፣ ከሱማ እስከ ላእላይ ግብፅ በአሉት ነገሥታት ላይ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ተብሎ ነገሠ። ስመ መንግሥቱም ምንይልክ ተባለ። አብረው ስለመጡና ስለ አገለገሉት ህዝቡን እንደ አረብ አበሺ፣ እንደግዕዝ አቡስ። ወታደሩ አግአዚኤል ተብሎ የሚጠራውን አምላክ እግዚአብሔር ብሎ አዲስ ስም አወጣ። 45፣ የጥንቷ ኢትዮጵያ ትንሣኤ ታሪክ፣ መራሪስ፣ 1985

ከሚኒሊክ ዘመን አስቀድሞ የነበሩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሕገ ኦሪትን ተቀብለው ዕውነተኛውን አምላክ እስቲያመልኩ ድረስ በፀሓይና በጨረቃ በክዋክብትም በእንስሳትና በአራዊትም በዛርና በክፉ መናፍስትም ያመልኩ ነበር እንጂ ፣ እንደ ሌሎች አሕዛብ እንጨት ጠርበው ደንጊያ አለዝበው ጣዖት ቀርፀው ወይም ወርቅና ብር አፍስሰው ምስል መስለው አያመልኩም ነበር። ቀዳማዊ ሚኒሊክ ወርዶ የኦሪትን ካህናት ይዞላቸው ከመጣ በኋላ ግን እየተማሩ በእውነትኛው አምላክ ብቻ አምነው ይኖሩ ነበር።    *14፣ ኅሩይ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ ከንግሥተ ሳባ እስከ ታላቁ የአድዋ ድል፣ 1927

በዚህ በ፲ኛው ፣ በ፱ኛውና በ፰ኛውም መቶ ዓመት ከክርስቶስ ልደት በፊት በሰሜን ኢትዮጵያ በኋላ የገነነውና አሁን ገናንነቱን በሐውልቱና በጽሑፉ የምናውቀው የአክሱም መንግሥት እስከአሁን አለመነሣቱን የሳባውያንና የአክሱምን ታሪክ የመረመሩት ሊቃውንት ሁሉ አረጋግጠዋል ። ከአትባራ ወንዝ ወዲያ በኑብያ ግን እነዚያው በኢትዮጵያዊነት የምንጠራቸው መጀምሪያ ነፃ ሆነው ፣ በኋላ እነቱትሞሲስ ቀጥሎም እነራምሲስ ፪ኛ ካስገበሩዋቸው ወዲህ አሁንም አንዳንድ ጊዜም እነሱ እያጠቁ ፣ አንዳንድ ጊዜም በግብፅውያኑ እየተገዙ ኑሯቸውን ይቀጥላሉ ።    *78፣ተክለፃድቅ መኩሪያ ፣ የኢትዮጵያታሪክ ፤ ኑብያ፡አክሱም ዛጉዌ እስከ ይኩኖአምላክ ዘመነመንግሥት ፣ 1951

የኩሽ ሕዝብ ፣ የሳባሕዝብ ፣ ነገደዮቅጣን ፣ ነገደአግዓዝያን ፣ ሂማሪያት ፣ ሳባውያን ፣ ሀበሳን እያለ በዝርዝር ሲጠራው ፣ ይህን ሁሉ ስም ደግሞ አቅፎ የሚገኘው ስም ኢትዮጵያ የተባለው ሥያሜ ነው ። ኢትዮጵያ ሲል በቀድሞ ዘመን ከግብፅ በደቡብ ፣ ከኤርትራ ባሕር ወደ ምዕራብ እስከ አትላንቲክ ድረስ ያለው አገር ሁሉ በሰፊው ኢትዮጵያ የተባለበት ጊዜ አለ ። ባንዳንድ ጸሐፊዎች ዘንድ ምሥራቁ ኢትዮጵያ ፣ ምዕራቡ ኢትዮጵያ ተብሎ ይገኛል ። ለናፓታ መንግሥት ብቻውን ለራሱ የኢትዮጵያነትን ስም ሰጥተውት ይገኛል ። በዚሁ ምክንያት ባለፉት ምዕራፎች እንደምናስታውሰው ግብፅን የገዙትን እነፒያንኪን ፣ እነሻባካን ፣ የቀድሞ የግሪክና የሮማ ጸሐፊ ሁሉ ኢትዮጵያውያን ናቸው ብለው ለግብፅ ግዛት 25ኛ ሥርወመንግሥት አድርገዋቸዋል ።   የናፓታንና የመርዌን ሕዝብ ግብፆችና አሶሮች ኩሽ ሲሉዋቸው ፣ ግሪኮችና ሮማውያኑ በብዙ ቦታ ኢትዮጵያውያን ብለውት ይገኛል ። *182፣ተክለፃድቅ መኩሪያ ፣ የኢትዮጵያታሪክ ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖአምላክ ዘመነመንግሥት ፣ 1951

ከውጭ እየመጣ የሚደረበው ሁሉ የራሱን ስምና ቋንቋ ይዞ በመኖር ፈንታ አብዛኛውን ጊዜ በፈታኞቹና በነባሮቹ ተውጦ ይገኛል ። በነዋሪው በካም ሕዝብ ላይ ነገደ ዮቅጣን የተባሉትን አግዓዝያን በየዘመኑ ገብተው በገዥነትም በነዋሪነትም በኢትዮጵያ ከተመሠረቱ ወዲህ በየጊዜው በነሱ ላይ የተጨመረው ሕዝብ ከየታሪኩ ሲለቅም የእስራዔል ፣ የከነዓን ፣ የፋርስ ፣ የሕንድ ዘር በየጊዜው በየምክንያቱ እየገባ እንደተጨመረ ይታወቃል ።     *183፣ ተክለፃድቅመኩሪያ ፣ የኢትዮጵያታሪክ ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት ፣ 1951

800 BC ኩሽ ከግብፅ በስተደቡብ በአሁኑ ሱዳን ውስጥ በአባይ ወንዝ ሸለቆ ይገኝ የነበረው አገር / ስርወመንግሥትና ህዝብ ስያሜ ነው ። የኩሽ ስርወመንግሥት የኑቢያ ስርወ መንግሥት በመባልም ይታወቃል ። የዚህ ስርወ መንግሥት የመጀመሪያው መቀመጫና መነሻ ከርማ ነው ። ይህ ስርወ መንግሥት በ2500 – 1567 ዓ .ዓ .ባለው ጊዜ እንደተነሳ ይገመታል ። ከ1567 – 1090 ዓ.ዓ. ባለው ጊዜ ከርማ በግብፅ ፈርዖኖች ቅኝ ግዛት አስተዳደር ሥር ወደቀ ። በዚህ ዘመን የተፃፉ የታሪክ ምንጮች አገሩን ኩሽ ይሉታል ።…. የኩሽ ስርወ መንግሥት በስምንተኛው መቶ ክፍለዘመን በተራው ግብፆችን ወርሮ 25ኛውን ስርወ መንግሥት በማቋቋም ሰፊ ግዛት መስርቶ ግብፅን ለሶስት አራተኛ ክፍለ ዘመን ያህል አስተደድሯል ።    *74 ,ተገኘ ፣ በራራ – ቀዳሚት አዲስአበባ ፣ 2020

በሚኒሊክ የጀመረው ከአይሁዳዊው የሀገረ መንግሥት ምሥረታ ማግሥት ጀምሮ አይሁዳዊው ባህል፣ ሥልጣኔና ዕምነት ማዕከላዊነትን ይዞ በኢትዮጵያ ተቀመጠ ። የኦሪት ህግና መንግሥት በአይሁዳዊነቱ በጥንታዊቷ ኢትዮጵያ ነገሠ ። በኢትዮጵያ የዛሬዎቹ ቤተ እስራዔላውያን ማንነት ምንጭም ከዚህ ዘመን አይሁዳውያን ወደ ኢትዮጵያ ካደረጉት ፍልሠት ጀምሮ የሚቀዳ ነው ። አይሁዳዊ አገዛዙ ጥቂት ምዕተ ዓመታትንም እንዳስቆጠረ የድዓማት ሥልጣኔ ዘመን ማዕከላዊነቱን ተረከበ ። ምንም እንኳ የድዓማት የሥልጣኔ ዘመን ተነስቶ የከሰመበት ወቅት በውል ባይታወቅም ፣ በቀይ ባህር ዳርቻ በድንገት የተፋፋመውን ንግድ የደቡብ ዓረቢያ የንግድ ሕዝቦችን ከፍተኛ ፍልሠት አስከተሎ በሠፊው አስተናገደ ።

800 BC ከአትባራ ወዲያ ያሉት የኑብያ ኢትዮጵያውያን ከሺ ስድስት መቶ ዓመት ወዲህ በግብፆች ተገዝተው ፣ ኢትዮጵያውያንም በ800 ዓ.ዓ. ከክርስቶስ ልደት በፊት መልሰው ግብፆችን የገዙበት ጊዜ አለ ። ነገር ግን እነዚህ ግብፅን መልሰው የገዙት የኑብያ ኢትዮጵያውያን እንጂ ሳባውያንና ሃበሳን አይደሉም ። ሳባውያንና ሃበሳን ከየመን ወደ ኢትዮጵያ ሰሜን የገቡበት ጊዜ የዛሬ ሊቃውንትና መርማሪዎች ከክርስቶስ ልደት በፊት ቢበዛ ፷0 ዓመት ግድም ላይ አድርገውታል ። ከዚያ በፊት ሥልጣኔና ፊደል የሌላቸው ሳባውያን ገብተው እንደሆነ አይታወቅም ። *34፣ተክለፃድቅ መኩሪያ ፣ የኢትዮጵያታሪክ ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት ፣ 1951

እንግዲህ እነዚህ ሁለት የግብፅና የኑብያ ኢትዮጵያ የጥንት መንግሥቶች ለየብቻ ንግድና ሥልጣኔ እየተለዋወጡ ሲኖሩ ፣ የአምልኮአቸውም ዓይነት ፀሃይዋን ፣ ዋርካውን ፣ ተራራውን ፣ ወንዙን (ዓባይን )፣ አሞራን በማምለክ ይመሳሰላል ። ለእነዚህም መሥዋዕትን ያቀርባል ። *35፣ተክለፃድቅ መኩሪያ ፣ የኢትዮጵያታሪክ ፤ ኑብያ፡አክሱም፡ዛጉዌ እስከ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት 1951

Page 1

የሶስት ሺ ዓመታት የኢትዮጵያ ታሪክ በጊዜ መስመር ላይ 

መግቢያ 

ጥንታዊ የግብፅ የፅሁፍ ማስረጃዎች እንደሚያሳዩትና በሌሎች ተመራማሪ ሊቃውንትም እንደታመነበት፣ የዛሬይቷ ኢትዮጵያና ኤርትራን ያማከለ “የፑንት ምድር” ወይም “የኩሽ አገር” ወይም ከጥናትዊ ግብፅ ጋር ሲተያይም “ደቡብ” በመባል በፈርዖናውያኑ ጭምር የታወቀች፣ ከአምስት ሺህ አምታት በላይ በቆየ መልኩ ግብፅ፣ ኢትዮጵያና የዛሬዋ ኤርትራ መካከል ጠንካራ የንግድ ገበያና ሽርክነት እንደነበራቸው ታሪካዊ ማስረጃዎች ይመሰክራሉ። የዝሆን ጥርስ፣ የተለያዩ እንስሳትና ቆዳቸው፣ የአውራሪስ ቀንድ፣ የኤሊ ቀፎ፣ ወርቅ፣ ዕንቁ፣ ሚይርህ፣ ዕጣን፣ ቅመማ ቅመሞች፣ የምግብ ሰብል ዓይነቶች፣ ጨውና ለባርነት አገልጋይ ህዝቦችን ጨምሮ ከኢትዮጵያ ወይም ግብፃውያኑ እንደሚሉት ደግሞ “የፑንት ምድር” ወደ ግብፅ፣ እንደ አዱሊስና ዘይላ ባሉ የቀይ ባህር ወደቦችን እና በሌላኛው አቅጣጫ ደግሞ የአባይን ወንዝ ራሱን የቻለ የንግድ መመላለሻ ጎዳና በማድረግ በንግድ ላይ የተመሠረተ የጥንታዊ ኢትዮጵያ አካል የሆነ የሥልጣኔ ዘመንን አሳልፈዋል። እነዚህ ጥንታዊ የንግድ እንቅስቃሴዎች የአፍሪካ ቀንዱ መልክዓምዳራዊ አቀማመጥን ማዕከላዊ ያደረጉ ነበሩ። በቀይ ባሕር ላይ ንግድ፣ ዕውቀትና ሥልጣኔን ይዘው የሚመላለሱ መርከቦች በአንድ በኩል የደቡብ ዓረቢያ፣ ህንድና የሩቅ ምሥራቅ አገራት የህንድ ውቅያኖስን መግቢያና መውጫ በር ሲያደርጉ፣ በሌላኛው በስተሰሜን በኩል ደግሞ ሜዲትራኒያን ባሕርን መናኸሪያው ያደረገው የመካከለኛው ምሥራቅና አውሮፓውያን አገራት የአፍሪካ ቀንዱን የንግድ መተላለፊያ ዋናው መንገዳቸው ላይ ተቀምጦ የሚገኝ ማዕከል ሆኖ አግኝተውታል። ይህም ማለት በቀይ ባሕር ላሉ ደሴቶች፣ በቀይ ባሕር ዳርቻ ላሉ ወደቦችና ውስጣዊ ከተሞቻቸው በኩል ጥንታዊው የኢትዮጵያና ኤርትራ ሕዝብ ለሥልጣኔና ሁሉም ዓይነት ውጪያዊ ዕድሎችና ክስተቶች እንዲጋለጥ አድርጓል።

አጠቃላይ ሥፍራው፣ በግሪክ ሮምና ሌሎች አውሮፓውያን ዘንድ ይህ ከኑብያ፣ ድዓማትና አክሱም ገናና ዘመን ጀምሮ ባሉት ወቅት በአፍሪካ የኢትዮጵያ ግዛት በመባል በአጠቃላዩ የታወቀው ምድር ከዛሬዎቹ ግብፅና ሊቢያ በስተደቡብ ጀምሮ ያለውን ሙሉ የአፍሪካ ቀንድ ምድርን ይዞ እስከ ዛሬዎቹ ታንዛኒያ ገደማ ድረስ የዘለቀ በአንድ የጋራ ኢትዮጵያ በሚል የወል ስም ይጠራ የነበረ ሰፊ ምድር ነው። የንግሥተ ሳባ ምድራዊ ግዛትም ይህ በቀይ ባሕር ዳርቻ ጨምሮ ያለውን ኢትዮጵያና ደቡብ ዓረቢያን ጭምርም ነበር።  ከንግሥተ ሳባ በኋላም፣ እንደዛሬውም ዘመን የየትኛውም አገር ነገሥታትና ሥርዓተ መንግሥታት ሁሉ፣ በየወቅቱ ሁነቶች በተቀያየሩ ጊዜ የግዛቶች መስፋትና መጥበብ አብሮ የሚከሰት ክስተት ነበረ። ከሳባና ኑብያ ወደ ድዓማት፣ ብሎም እስከ አክሱማዊው መንግሥት ባለው የኢትዮጵያ ሃገረመንግሥት ጉዞ ላይ የኑብያ ኢትዮጵያዊው ምድር በግብፅ ፈርዖኖች መዳፍ ውስጥ በቅኝ ግዛት የተያዘ፣ አንዳንዴም ከግብፆች ነፃ ወጥቶ ግብፅን መልሶ ለመግዛት የበቃበት ወቅት ነበር። ፈርዖኖቹ የጥንታዊ ኢትዮጵያ አካል የነበረችውን ኑብያና ጥንታዊ ከተሞቿን ከርማ፣ ናፓታ እና መርዌን ጨምረው ሲገዙ ኢትዮጵያ ተብሎ ከሚጠራው አንድ ምድራዊ ግዛት ላይ ወስደው ነበር። ቀጥሎም ግን በቀጣይ ትውልድ እንደ ፒያንኪ እና ታርሐቃ ባሉ ኢትዮጵያውያን የኑብያ ነገሥታት ግብፃዊ ፈርዖኖች ተገርስሰው የኑብያ ኢትዮጵያውያኑ የግብፅ ሃያ አምስተኛው ሥርወ መንግሥት በመባል ታውቀው ለሰባ አምስት ዓመታት ገደማ ግብፅን ገዝተው ማለፋቸውን ታሪካዊ ማስረጃው ዘግቦታል። በንፅፅር፣ ይህም እንደገና ከክርስቶስ ልደት በኋላ በአምስተኛው ክፍለዘመን በአክሱም የነገሠው ካሌብ የተባለው ኢትዮጵያዊ ንጉሥ ቀይ ባሕርን ተሻግሮ ዛሬ የመን የሆነውን የደቡብ ዓረቢያን ምድር በወረራ አስገብሮ እንደገዛ በተመሳሳይ ሁኔታ ታሪክ ከአስቀመጠው ጋር ተመሳሳይ ክስተት ሆኖ ይገኛል።

ከእነዚያ ከመሳሰሉት ጊዜያትም ጀምሮ፣ በኢትዮጵያ የሀገረ መንግሥትና የሥርዓተ መንግሥት ረጂም የምሥረታ ሂደትም፣ አቅጣጫ ቀያሪና ዘዋሪ የሆኑ ብዙ ሕዝባዊ ክስተቶች፣ ፍልሰቶችና ሠፈራዎች በውህደት ተከስተዋል። ኑብያና ሌሎች የጥንታዊ ኢትዮጵያ የግዛት አካላት ከሔዱት ቢቆጠሩም፣ የሃበሻ ምድር በመባል የሚታወቀው ሕዝብና ወገኖቹ ግን ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን በስም ሆነ በይዘት በዘመናት መካከል ይዞ እየተጓዘ ከድዓማት ወደ ሳባውያንና አክሱም፣ ከአክሱም ወደ ዛጉዌ፣ ከዛጉዌ በይኩኖ አምላክ አስቀጣይነት እስከ ዘመነ ኃይለሥላሤ፣ ከዚያም ወደ ደርግ፣ ከደርግ ደግሞ እስከ ዘመነ ኢህአደግ ድረስ ቀጥሎ ሥነ መንግሥታዊ ስሙንና ተቋሙን ይዞ እስከ አሁኑ የብልፅግና ፓርቲ ሥርዓተ መንግሥት ድረስ መጥቶኣል።

የመንግሥታዊና ሃገራዊ ግንባታ ሂደቱ ሁሌም የሚካሄደው በየዘመኑ ከሚከሰቱ የፖለቲካ ሥልጣንን ተቆጣጥረው የአገረ መንግሥት ምሥረታ ሂደቱን አቅጣጫ ቀያሪና ዘዋሪ ወይም ተፅዕኖ ፈጣሪ በሆኑ መሪዎች አመካኝነት ነው። እነዚህ መሪዎች በየጊዜው ከነባሩ ሕዝብ ዘንድ በከፊል ቅቡልነትና ኢትዮጵያዊ ውህደትን በማረጋገጥ የሚያስቀጥሉ፣ ኢትዮጵያዊ ሀገረ መንግሥት ምሥረታን ያሳለጡ ለየዘመናቸው ስኬታማ መሪዎች ወይም ሥርዓቶች ናቸው። መሪዎቹ ከባዕድም ሆነ ከጎንዮሽ የሚመጡ ሃሳቦችን፣ ዕምነቶችን እና ሕዝቦችን ተቀብለው በማስተናገድ በኢትዮጵያዊነት ስም የሚያዋህዱም ነበሩ። የአይሁዳውያንን፣ የዓረቦችንን፣ የአውሮፓውያንን፣ የህንድና ሩቅ ምስራቆችን እንዲሁም የጎረቤት አፍሪካውያንን ፍለሰትና ውህደትን ኢትዮጵያ በስኬት ስታስተናግድና ኢትዮጵያዊነትን ስትገነባበት ቆይታለች። በዕምነትና ባህልም ረገድ ኢትዮጵያ የአይሁድ ፣ ክርስትና እና እስላም ዕምነቶችን ተቀብላ የዓለማችን ሶስት ታላላቅ ጥንታዊ ሀይማኖቶችን የራሧ አድርጋለች። በዘር ገመድም ቢሆን ከጅምሩ የካምና ሴም ነገዶችን እያዋሃደ መጥቶ፣ በተለይም ዛሬ የሃበሻ ሕዝብና አገር በመባል ለቆየው ውህድና ቅይጥ ሕዝብ በዛሬው ኢትዮጵያዊነት ላይ የመሠረታዊ ሥሪቱ አስኳል ሆኖ ሊታይ በቅቷል።

የኢትዮጵያን ታሪክ ከመጨረሻው 3ሺ ዓመታት ብቻ ጀምረን ስናይ፣ ተወደደም ተጠላ የንግሥተ ሳባና ንጉሥ ሠለሞን ትርክት አይተኬ መነሻው ሆኖ ተቀምጧል። ከመካከለኛው ምሥራቅ የተነሳው በቀዳማዊ ሚኒሊክ ምክንያትነት የአይሁዳውያን ወደ ምድረ ኢትዮጵያ መፍለስ እንደ ማሳያ በኢትዮጵያ ከመጀመሪያዎቹ አንዱ ነበር። ይህም በኋላ ላይ የቤተ እሥራዔላውያን ወይም የፈላሾች የወደ ኢትዮጵያ የተደረገ ፍልሠትና ውህደት ታሪክ አካል ሆኖ እናገኘዋለን። ዛሬ ቤተ እስራዔላውያኑ እናት አገር ወደሚሉት እስራዔል በከፊል ሂደው ቢኖሩም፣ እነዚያ አይሁዳውያን ዕምነታቸውን ይዘው ከነባሩ ኩሻዊ ነገድ ጋር በመቀላቀል ለዘመናት በኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት የኢትዮጵያዊነትን አገረ መንግሥት ግንባታ መሥራች አካል ሆነው መሠረት ጥለዋል። ቀጥሎም ከደቡብ ዓረቢያ የተነሱት በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ የነገደ ዮቅጣን የሴም ዘርነት ያላቸው ዓረቦች በአዶሊስ፣ አክሱምና ሌሎች የቀይባህር ዳርቻና ውስጣዊ ሥፍራዎችን የንግድ ማዕከላትን መሰረት አድርገው ኖረዋል። እነዚህም መጤ ፈላሽና ተዋሃጅ የደቡብ ዓረብ ሕዝቦች በውህደታቸው ኢትዮጵያዊነትን ከአዳበሩ አካላት መሀል ከዋነኞቹ አንዱ ሆነው አልፈዋል። ሕዝባዊም ባይሆኑ ከዓረቦች መካከልም የተገኙ ሌሎች ብዙ ተፅዕኖ ፈጣሪ አውሮፓውያን፣ የአርመኒያ፣ ህንድና፣ የእስያ ዜጎችም በውህደታቸው ኢትዮጵያዊነትን ከአዳበሩ አካላት መሀል ነበሩ። እንደማሳያ የአክሱም ነገሥታት በግሪክ ቋንቋ ዕውቀታቸው በጣም የተካኑ መሆናቸው የአውሮፓውያን መጤዎችን ታቃፊነት ጭምር ማሳያ ሊሆን ይችላል። ከዚያ ብዙ ቆይቶም ደግሞ፣ በግራኝ አህመድ ጦርነት ማግስት በ16ኛው ክፍለ ዘመን፣ ራሱን ከነገደ ኩሽ የሚመድበው የኦሮሞ ጎሳና ህዝብ ከበረይቱማና ቦረን ከሚባል ከዛሬው ሶማሊያ፣ ኬንያና ኢትዮጵያ ድንበር ገደማ ተቀላቀለ።  ባልተቋረጠ የጥቂት መቶ ዓመታቶች ፍልሠት በዛሬይቷ ኢትዮጵያ ዘመቻ በሚመስል መልክ በተስፋፊነት ውስጣዊ የኢትዮጵያ ግዛቶችን በመጤነት ሠፍሮ ዛሬ የሚገኝባቸውን ግዛቶች ሁሉ ላይ ኢትዮጵያዊነትን የራሱ አድርጎ ከሌሎች ወገኖቹ ጋር በኢትዮጵያዊ ውህደት ውስጥ ለመገኘት በቅቷል። ምናልባትም ከቦረና አና በረይቱማ በስተቀር፣ ከ13 ኛው ክፍለዘመን በፊት በዛሬይቷ ኢትዮጵያ ካርታ ውስጥ ለመኖራቸው ምንም ዓይነት ማስረጃ የማይገኝላቸው የኦሮሞ ጎሣ ሕዝቦች ወደ ዛሬይቷ ኢትዮጵያ መሀል ምድር ወረራ በሚመስል የሕዝባዊ ፍልሠት ዘመቻ በማካሄድ ከነባሩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ተቀላቅለዋል። ሂደቱ እጅግ ብዙ ዋጋዎችን ያስከፈለ ቢሆንም በመጨረሻ ግን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ውህደትን የፈጠሩ የኦሮሞ ጎሣ ሕዝቦች ያለ ጥርጥር የኢትዮጵያዊ ሀገረ መንግሥት ምሥረታው አካል በመሆን በኢትዮጵያዊ ውህደትና አገረመንግሥት ግንባታውም ከፍተኛ ድርሻቸውን አበርክተዋል። የታላቁ ምሑር ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ “የአባ ባሕርይ ድርሰቶች – ኦሮሞችን ከሚመለከቱ ሌሎች ሰነዶች ጋር” በሚባለው መፅሃፋቸው በገፅ 167 ላይ የሚከተለው ተቀምጧል። “በ16ኛው ምዕተ ዓመት ኢትዮጵያን የወረሩ ኦሮሞዎችና ሊከለክሏቸው የሞከሩ የቀድሞዎቹ ነባሮች ሁሉም ከሞላ ጎደል እኩል አያቶቻችን ሆነዋል። እኛም እንደዚያው ከሞላ ጎደል እኩል ልጆቻቸው ነን። “ ይህ አባባል ቢያንስ ሁሉንም የሚያስማማ ሃሳብ ይመስላል።

በመጨረሻም ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በመዋሃዱ ክስተት ሳይጠቀስ የማይታለፈው ሕዝባዊ ፍልሠት የራስ ተፈሪያኖቹ ጥቁር ሕዝቦች ነው። ዛሬ ምናልባት የመጨረሻ በሚባል ከነባሩ የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ፍልሠትና ውህደትን ለማካሄድ እርምጃ የወሠዱ ህዝቦች ቢኖሩ የጃማይካ፣ ካሪቢያንና ሌሎች ጥቁር አፍሪካዊያን በሻሸመኔና አካባቢዋ የሠፈሩ ኢትዮጵያዊነትን የተቀላቀሉ ሕዝቦች ናቸው። በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሤ ፈቃድና ትዕዛዝ በኢትዮጵያ የቦታና ዜግነት ስጦታን የተቀበሉት እነዚህ የዘመናችን የመጨረሻዎቹ የራስ ተፈሪ ዕምነት ተከታዮች የወደ ኢትዮጵያዊነት ፍልሠትና ውህደት ስኬታማ ህይወት መምራት መቻላቸውን ግን አንባቢያን እንዲፈርዱ ተጋብዘዋል ። በድምሩ ግን፣ ጥንታዊ የሆነው የእነዚህና ሌሎች መጤ፣ ነባርና ውህድ ሕዝብ ኢትዮጵያዊ የሚለውን ጥንታዊ የወል መጠሪያ ስም ተጋርተው በትውልድ ቅብብሎሽ የኑብያ፣ የድዓማትና የአክሱም የሥልጣኔ ዘመን በመባል ታውቀል። የኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ሥሪት የሚቀዳውም ከእነዚህ ሁሉ የሕዝቦች ውህደትና ውጤት ነው።ተወደደም ተጠላ፣ ባለረጂም ዕድሜው ትርክትና ትውፊቱ እንደሚያመለክተው በኢትዮጵያ ሥነ መንግሥት ምሥረታ ሂደቱ ውስጥ የሰሎሞናዊና የዛጔዌ ሥርወመንግሥታት የተባሉት ዋነኞቹ መሪዎች ነበሩ። ይህም የነገሥታት ሥርዓተ መንግሥት አካሄድ እጅግ ጥንታዊ የሚባል ጊዜውን ያዋጀ የአገረመንግሥት ግንባታ ይዞታና አካል በመሆኑ ዛሬም ቢሆን ታሪካዊ ትርጉም ሰጪነቱ ግዙፍ ነው። ኢትዮጵያዊ ማንነትና ስያሜን ይዞ፣ የራስ አድርጎ ለዛሬው የግንባታ ሂደት ዘመን መድረስ የጥቁር ሕዝቦች ኩራትና ደስታ ምንጭ ነው። ለዛሬው ትውልድ፣ አድዋም የዚህ ኩራትና ደስታ አንዱ ማሳያ ምሳሌ ነው። ውስጣዊ አንድነትና ፍትሃዊ ዕኩልነት የሰፈነባት በነገሥታቱ አገራዊ የግዛት ይዞታ ስሜትና ፍላጎት ልክ የሚወዳደር እርስበእርሱ ወደከፍታ ለመውጣት መስራት የምትችል አዲስ ኢትዮጵያን መፍጠር ግን የአሁኑ ትውልድ ድርሻ ይሆናል። ዛሬ የሚታየው ስጋት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ስምና ግንባታ ሂደት የመሰናከል አደጋ ነው።
እንግዲህ የዛሬይቷ ኢትዮጵያ ለዛሬ ማንነቷና ቁመናዋ የበቃችው አያሌ የባዕድ አገራትና የአገር ውስጥ ፈተናዎችን በማለፍ እንደማንኛውም የዓለም አገራት፣ ሲመቻት በግዛትና ኃይሏ እየተስፋፋች፣ ሳይመቻት እየጠበበች ነበር። በፖለቲካና በኤኮኖሚ ኃይል የበላይነትን ሁሌም ለመያዝ አገራትና ቡድኖች የሚያደርጉት ትግል የማያቋርጥና ተፈጥሮአዊ የሚመስል የሰው ልጆች ታሪክ ነው። በዚህ መሃል መልካምድራዊ አቀማመጧም ቢሆን የራሱ ጥቅምና ጉዳትን በየጊዜው ለሕዝቧ ይዞ መገኘቱን ማስተዋል ያስፈልጋል። የክርስትና እና እስልምና ሃይማኖት የተስፋፊነት ባህርይ፣ የግዛት ሥልጣንና የመሬት ይዞታ ሃብትን በበላይነት ለመያዝ በዘመናት መካከል የተደረገው የአገር ውስጥ ተገዳዳሪ አካላት ትግልም ያልተቋረጠ ነበር።

ይሁን እንጂ በአሁኑ ወቅት ግን የዛሬይቷ ኢትዮጵያ አራት ዋና ዋና ተግዳሮቶች፣ ሲከፋም ጠላቶች ይታዩባታል። ሁሉም ሕዝቦቿ በእኩል ፍትሃዊ ተጠቃሚነት፣ በበቂ ጤና እና ደስተኛነት ዜጋ ሁሉ ፍላጎቱ መሰረት የሚኖርባት አገር እንዳትሆን የሚያግዷት በአራት ዋና ተግዳሮቶች ወይም ጠላቶቿ ምክንያት ነው ብሎ ይህ መድረክ በጥብቅ ያምናል። እነዚህም አራት ዋና ጠላቶቿ፤ 1ኛ) ድህነት፣ 2ኛ) በዜጋ ደረጃ፣ እውነትንና የሳይንሳዊ ዕውቀትን መሠረት ያላደረገ ዕለታዊ መርህና ትኩረት፣ 3ኛ) ጠንካራ አንድ ሃገራዊ አንድነትንና በፍትሐዊ እኩልነት ላይ ትኩረት ያደረገ ዕውነተኛ ዕድገትን መሠረት ከሚያደረግ አገራዊና ሕዝባዊ የአደረጃጀት መርህ ይልቅ፣ በጠባብና ኋላ ቀር የጎሣ ብሔርተኝነት ላይ ተመሥርቶ የነገሠው ቡድናዊ የፖለቲካ ሥልጣንን የተጠማ የከፋፍለህ ግዛው የጥቂቶች ጥቅምን ብቻ አስከባሪ ዕሳቤና መርህ 4ኛ) የባዕድ አገራትን ብሔራዊ ጥቅም ተቃርኖና ተፅዕኖ በጥበብ ይዞ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ብሔራዊ ጥቅም ጋር በብልሃት አግባብቶ የማስተዳደር ብቃት ያለመኖር ወይም ዕሳቤዎች ናቸው።

ለመነሻ በአጭሩ መፍትሄውም እንደሚከተለው ነው ተብሎ ይታመናል። ድህነትን መዋጋትና ማሸነፍ የሚቻለው የኢትዮጵያ ሕዝብ በጠንካራና ታታሪ ሠራተኛነትና ምርታማነትን በዘለቄታው በማስቀጠል ነው። በመጀመሪያ የምግብ ዋስትናን በመላው አገሪቱ የሚያረጋግጥ ሥራ መሥራትን ይጠይቃል። በምግብ አቅርቦት ራስን መቻል እንደ ግለሰብም ሆነ እንደአገር ክብርና ህልውናን ያረጋግጣል። ምርትና ምርታማነት በመላው ኢትዮጵያ ለሕዝቦቿ በእኩል ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የዘመኑን የቴክኖሎጂ ማምረቻ ተቋማትን በሠፊው መገንባት የሚያስፈልግ ሲሆን፣ ይህም ሌላውን ግዙፉ የሥራ አጥነት ቀውስ ለመቅረፍም በቀጥታ ይረዳል። በምግብ ዋስትና ያልተቋረጠ ቀውስ ምክንያት የዛሬይቷ ኢትዮጵያ በምጣኔ ሃብት ደረጃ ከዓለማችን የድሃ ድሃ ተብላ የምትመደብ አገር ነች። ለዚህ አጭር ማሳያውም ሕዝቦቿ በዓለም ቋሚ የምግብ ተረጂ አገር መሆኗ ነው። ቀጥሎም ሥራ አጥነትና የመልካም አስተዳደር አለመኖር ተጨማሪ ማሳያዎች ናቸው። እንደ ንፁህ ውሃ የኤሌክትሪክ ኃይል ችግሮችና ሌሎች እንደ መኖሪያ ቤትና የትራንስፖርት አገልግሎት ችግሮች ሁሉ የመሠረታዊ ፍላጎቶች ተደራሽነት ችግሮች ሲሆኑ፣ የኢትዮጵያን ድህነት መለኪያዎች ናቸው። ስለዚህም ይህ እጅግ ከፍተኛ አገራዊ ትኩረትና የቅድሚያ ቅድሚያ መሆን ያለበት ጉዳይ ነው።

ቀጥሎም አገራዊ የሥነ ባህርይና ሥነምግባር ምርመራና አዲስ ባህላዊ እድሳት ላይ አቋም በመውሰድ ዕውነትንና ሃቀኛ ባህርይን ብቻ መላበስም ዜጋዊ ግዴታ ሊሆን ይገባል። ዕውነትን ሁሌም በመናገር መኖር፣ ለህሊና መገዛት፣ ተጠያቂነትንና ፈርሃ እግዚአብሔርን በፅናት ይዞ መኖር ዛሬውኑ አስፈላጊ ነው። ዕውነትን ብቻ በመናገርና በሀቀኝነት መኖርን መመረጥ ዜጋዊ ግዴታ መሆኑ እጅግ ወሳኝነት አለው። ከዚህ በተያያዘም፣ ከፍተኛና የማይቋረጥ የሳይንሳዊ ዕውቀትና ዕድገት ትኩረት፣ እንዲሁም ለሁሉም ዜጎች እኩል ፍትሃዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ የአስተሳሰብ መንገድን መከተል ነው። በማንኛውም ዕለታዊ ህይወት ውስጥ ሀቀኝነት እንዲሁም ሳይንሳዊ ዕውቀትና ጥበብ በመርህ ደረጃ ሕዝባዊ መመሪያ ሊሆኑም ይገባል። ዛሬ ከምድር በታችም ሆነ ከምድር በላይ ያሉ የሃብት መፍጠሪያ የዓለማችን የሃብትና ሃይል ምንጮች እያደረቁና አሻሚነታቸው እየተጧጧፈ ከመጣ ቆይቷል። ስለዚህ በአገራት መካከል ያለውን ሽሚያ ተወዳድሮ የሃብትና ሃይል ምንጮቹን ተጠቃሚ ለመሆን ኢትዮጵያዊ አንድነት ላይ መሠረት መጣል ከመቸውም ጊዜ በበለጠ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው። ምክንያቱም በጎሣና በጠባብ ብሔርተኝነት ተበጣጥሳ የተገኘች አገር እንኳን በዓለም አቀፍ መድረክ በዕውቀትና ሃብት በዓለም አቀፍ ብቃት ደረጃው ተገዳዳሪ የተጠቃሚነት አቅም ሊኖራት ይቅርና ራስን በምግብ የመቻል አቅሟ ጨርሶ የሚጠፋ ይሆናል። ኢትዮጵያውያን ያላቸውን የተፈጥሮና ቅርሳዊ ሃብት በዳበረ ሳይንሳዊ ዕውቀት በርብርብ መዋጮ ለዓለም አቀፉ መድረክ ተገዳዳሪ መሆን ይጠበቅባቸዋል። ከዚህ ያነሰ ግን፣ ያለፉት 32 ዓመታቱ የጎሳ ብሔርተኝነት መርህ እንዳስከተለው አገራዊ ቀውስና ጥፋት ሁሉ ለቀጣይ የውድቀት ጉዞ የሚዳርግ ነው። የዘመኑን በቴክኖሎጂ የዳበረ የማምረቻ ተቋማትና መሣሪያዎችን በላቀ ስፋት መጠቀም መጀመር የሚቻለው፣ ሕዝቡ በዕለታዊ ዕውነተኛነትና የሳይንሳዊ ዕውቀትን መንገድ የሙጥኝ ማለትን ሲችል ነው። በመጨረሻም፣ የባዕድ አገራትን ብሔራዊ ጥቅም ከኢትዮጵያ ህዝብ ብሔራዊ ጥቅም ጋር ተቃርኖን አለዝቦና በጥበብ አዛምዶ ይዞ መኖርን መምረጥ እንደማንኛውም ብልህ አገር ተመራጭ መርህ ሊሆን ይገባል። ይህ በከፍተኛ ጥንቃቄና አርቆ አስተዋይነት ቢታሰብበት አዋጭ ምልከታ ነው። ኢትዮጵያን ካለ ባዕድ አገር ጠላት ማኖር ይቻላል ብሎ መሥራት ያስፈልጋልና። ይህ የመድረካችን እይታ በአጭሩ ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ውድቀትና ስኬት ምክንያቶች ከሆኑት ግምቶች ውስጥ ዋኖቹን በአጠቃላይ አገናዝቦ የያዘ የዚህ መድረክ እይታ ነው።

እንደ ተጨማሪ መፍትሔም፣ ጥንታዊው የኢትዮጵያ ታሪክ ለዛሬው ትውልድ እጅግ አስፈላጊና አይተኬ የኢትዮጵያዊ ዜግነት ሥነልቦና እና የአዕምሮ ጥንካሬ ምንጭ ነው። ተዘጋጅቶ የተቀመጠውን ጥንታዊ የታሪክ ማንነት እንዳለ በዕድለኝነት ተቀብሎ ሊጠቀመበት ያልቻለ ትውልድ ተጎጂ እንጂ ተጠቃሚ አይሆንም። የአገር ውስጥ የመንግሥታዊ ሥልጣን ጥመኛ ዓላማ ይዘው የሚገኙ ሁሉ የሕዝብ ሰላምና ዕድገት እንዳይመጣ ዕንቅፋቶች ናቸው። እንዲሁም በባዕድ አገር የኢትዮጵያ ጠላቶች ምክንያት የዛሬው ትውልድ ሙሉ መብቱ ተነፍጎና ነፃነቱ ተረግጦ ቢገኝ ሊታዘንለት የሚገባም ትውልድ አይሆንም። ይህ መድረክ በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ መልካም ታሪክ ወይም ትርክት ከሀብትና ወታደራዊ ኃይል ይልቅ እጅግ የላቀና ረጂም ዕድሜ ያለው የአገራዊ አንድነት ኃይል ምንጭ ነው ብሎ በፅናት ያምናል። በተቃራኒው መጥፎና መሠሪ የሃሰት ታሪክም እንደ ትርክት እጅግ አደገኛ ጥፋትን የሚስከትል እንደሆነም ያምናል። ስለሆነም ዛሬ ተወደደም ሆነ ተጠላ፣ የሶስት ሺህ ዓመታት የኢትዮጵያ አገረ መንግሥት ምሥረታ ሂደትን መልካም ታሪክ ወይም ትርክት የኔ ያለው የሰለሞናዊው ሥርወመንግሥት አካል፣ የንግሥተ ሳባና ንጉሥ ሰለሞንን ትርክት እንደመነሻ መልካም ትርክቱ አድርጎ የኢትዮጵያ ሕዝብ የራሱ ታሪክ አካል አድርጎታል። ይህ በጊዜ ሂደት የተፈተነ ነገሥታት መራሹ ኢትዮጵያዊ የአገረመንግሥት ግንባታ ለዛሬው ትውልድ ልዩ የሥነ ልቦና ጥንካሬ ልዩ ጥቅም አለው። በእርግጥም የመጨረሻው የሶስት ሺህ ዓመታት የኢትዮጵያና ሥነመንግሥታቷ ታሪክ በዓለማችን እጅግ አስደማሚ ከሚባሉ ትርክቶች ውስጥ አንዱ ሆኖ ተቀምጧል። ይህ ቀዳማዊ ሚኒሊክን አሃዱ ንጉሥ ያደረገው የንግሥተ ሳባና ንጉሥ ሰለሞን የሥነመንግሥት ትርክት እንደመነሻ ዕውነተኛም ሆነ አፈታሪክ፣ በልዩ ሁኔታ ኢትዮጵያዊ አገረመንግሥትን በአዲስ ታሪካዊ መልክ ከመገንባት አንፃር እጅግ ጠንካራ ጠቃሚነቱ ግልፅ ሆኖአል። ከፍትሃዊ እኩልነትና ተጠቃሚነት አኳያ እንከን የለሽ ሥነመንግሥት ባይሆንም በአፍሪካ ቀንድ እንደአገር ልዩ ክብርና ዕውቅናን በዓለም ዙሪያ ያተረፈች አገር እንድትፈጠር አድርጓል። ይህም ትርክት ይባል ዕውነታ በፅሁፍ ከተቀመጠና ለዘላቂና ጠንካራ ሀገረመንግሥት ግንባታ ጥቅም ላይ ከዋለ በእርግጠኝነት ከ700 ዓመታት (በአክሱም በ1314 የወጣው ክብረ ነገሥት በተባለው መጽሃፍ ታሪክ) በላይ ዕድሜን አስቆጥሯል። ይህም በጊዜ ሂደት የተፈተነ የኃይል ምንጭነቱን በተግባር አረጋግጧል። ይህ ታሪክ ከሌሎች የኢትዮጵያ ታሪኮች ጋር ተደምሮ በጊዜ መስመር ላይ እንደሚከተለው ተቀምጧል።

 PAGE 1 – END